ደብረ ታቦር

ይህ በዓል በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ የሚከበር ሲሆን ጌታችን መድሃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ አያሰተማረ በነበረበት ዘመን በደብረ ታቦር ላይ ብርሃነ መለኮቱን ክበረ መንግስቱን የገለጸበት እለት ነው። /ማቴ ፲፯፥፩/
ይህ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች ዘንድ ልዩ ስም አለው ቡሄ ይሉታል ቡሄ ማለት መላጣ ገላጣ ማለት ሲሆን ይህን ስያሜ ያገኘው ክረምቱ አልቆ ደመናው ተገልጦ ብርሃን የሚታይበት ጊዜ ስለሆነ ነው ተብሎ ይነገራል። ነገር ግን የደብረ ታቦር ምስጢር የተገለጸው በፍልስጥኤም ደመና በማይታይበት በበጋ ወራት ነው።

    በኢትዮጵያዊያን ባህልም እናቶች ዳቦ ወይም ሙልሙል በመጋገር ልጆች ደግሞ ጅራፍ በመግመድ ተጠምደው ይሰነብታሉ በበዓሉ ዋዜማም በነሐሴ ፲፪ ሕፃናት በየ አካባቢያቸው ቡሄ በሉ ልጆች ሁሉ
                                              ቡሄ መጣ ያ መላጣ
                                              ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ። በማለት ሲያዜሙ ያመሻሉ። በዚህም ጊዜ እናቶች ያዘጋጁትን ሙልሙል ወይም ዳቦ ይሰጧቸዋል። ልጆቹም ያንን አየገመጡ የገመዱትንም ጅራፍ ሲያጮሁ  ያመሻሉ ይውላሉ። ይህንንም ሲያደርጉ ካለምክንያት አይደለም የጅራፉ ጩኸት የድምጸ መለኮት ሲሆን ጅራፉ ሲጮህ ማስደንገጡ ደግሞ የሐዋርያትን ማለትም ጴጥሮስ ያዕቆብና ዮሐንስ ድምዐ መለኮትን ሲሰሙ መደንገጣቸውን በግምባራቸው መደፋታቸውን ያስታውሳል። በአንዳንድ አካባቢዎችም የቡሄ እለት ችቦ ይበራል ይህም በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃን ተምሳሌት ነው የሚሉ አሉ።
   የአብነት ወይም የቆሎ ተማሪዎችም ከበዓሉ ቀደም ብለው እየዞሩ ከመንደርተኛው እህሉንም ብቅሉንም ጌሾውንም እየለመኑ በወንድ እጃቸው ዳቦውን ጋግረው ጠላውን ጠምቀው ቆሎውንም ቆልተው ሊያስቀድስ የመጣውነ ህዝብ በሙሉ ያበላሉ ያጠጣሉ። ህዝቡም ይህንን ስለሚያውቅ በሚለምኑበት ጊዜ እህሉን በገፍ ይሰጣቸዋል።
 በዚህም በዓል የሃገራችን ሰዎች ዘመድ መጠየቂያ ጊዜ ነው። በልጆች ቁጥር ዳቦ ተይዞ ዘመድ ከዘመዱ ወዳጅ ከወዳጁ ይጠያየቃል ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት ቡሄን ከዋሉ የለም ክረምት በሚል ስነቃል ይመስላል ወገን ወገኑን የሚጠይቀው።
እኛስ እንዴት እያከበርነው ይሆን? መልሱን ለእናንተ።

Comments

Post a Comment

Popular posts from this blog

ቅዱስ ያሬድ ማነው? ከዳንኤል ክብረት

መጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ፬ የሐዲስ ኪዳን መግቢያ

መጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ፪